አዲሱ ደምሴ ወደ ቺካጎ ዩኒቨርስቲ ፖለቲካ ኢኒስቲትዩት አቅንቷል

የጆ ባይደን ፕሬዝደንታዊ ምርጫ አማካሪ የሆነውና በቅርቡ የተከናወነውን የዲሞክራቶች ኮንቬንሽን በሀላፊነት ያዘጋጀው አዲሱ ደምሴ በዚህ ወር ወደ ቺካጎ ዩኒቨርስቲ ፖለቲካ ኢኒስቲትዩት አቅንቷል፡፡

ወደዚያ የተጓዘውም የዩኒቨርስቲው የ2020 ሬዚደንት ፕሪትዝከር ፌሎው ተመራጭ ሆኖ ነው፡፡ ዩኒቨርስቲው እንዳስታወቀው በየሩብ አመቱ የተለያዩ በፖለቲካው አለም ያሉ ሰዎችን መርጦ ይጠራቸዋል፡፡ የሚጠራቸውውም የመንግስት ባለስልጣናትን፣ ፖሊሲ አውጪዎችን፣ ዲፕሎማቶችን፣ አክቲቪስቶችንና ጋዜጠኞችን እንደሆነ የገለፀው ዩኒቨርስቲው የሚመረጡት ሰዎች ተማሪዎችንና የፖለቲካ ፋክልቲውን በማግኘት ንግግር እንደሚያደርጉ አስታውቋል፡፡

በተጨማሪም በወቅታዊ የፖለቲካና የፖሊሲ ጉዳዮች ላይ ለተማሪዎች ስልጠና እንደሚሰጡ አመልክቷል፡፡ ዘንድሮ ከተመረጡት ውስጥ አዲሱ ደምሴ አንዱ ሲሆን ሌሎች አራት ጋዜጠኞና ፖለቲከኞች አብረውት በመመረጣቸው ወደ ቺካጎ አቅንተዋል ሲል ታዲያስ የኢንተርኔት መፅሄት ዛሬ ዘግቧል፡፡