በመለስ ዜናዊ አካዳሚ ስም በአዲስ አበባ የተሰራው ህንጻ ሆስፒታል ሊሆን ነው

ከጅጅጋ እስከ ባህርዳር፤ ከአፋር እስከ ወለጋ፤ ከጎንደር እስከ ቀብሪዳር፤ ከጋምቤላ እስከ ቤኒሻንጉል፤ ከደብረማርቆስ እስከ ሐረር በመለስ ዜናዊ ስም የተሰየሙ ፓርኮች፣ ትምህርት ቤቶች፣ ሆስፒታሎች እና ወዘተ ስማቸው ላለፉት 3 ዓመታት እየተፋቀ በሌላ ሲቀየሩ ቢቆይም በአዲስ አበባ በመለስ ዜናዊ ስም ያሉ ነገሮች ሳይነኩ ቆይተዋል።

አሁን ግን ጊዜው እየደረሰ ይመስላል። በአዲስ አበባ በመልስ ዜናዊ አካዳሚ የተሰራው ሕንጻ ለ እናቶች እና ህጻናት ልዩ ዘመናዊ ሆስፒታል እንዲሆን ተወስኗል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የህንጻውን ዲዛይኑን በማሻሻል ወደ ሆስፑታነት እንዲቀየር እያስደረገ ይሆን ይህም በአጭር ቀናት ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆን የዘ-ሐበሻ ምንጮች ገልጸዋል።

በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች በመለስ ዜናዊ አካዳሚና መለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን ስም የተመዘገቡና ታጥረው የተቀመጡ ቦታዎች ይገኛሉ። እነዚህን ቦታዎች ምን ለማድረግ እንደታሰበ ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ የለም።

ወ/ሮ አዜብ መስፍን የሕወሓት ነባር ታጋይና የቀድሞው የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ ባለቤት ናቸው። ቀዳማዊ እመቤት በነበሩበት ወቅት የትግራይ መልሶ ማቋቋሚያ ማኅበር (ትዕምት ወይም ኤፈርት) መሪ ነበሩ። ወ/ሮ አዜብ፤ የባለቤታቸው መታሰቢያ የሆነው የመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን መስራችና የቦርድ ሰብሳቢም ናቸው። በአሁኑ ሰዓት አዜብ መስፍን ከመለስ ዜናዊ ፋውንዴሽን ስራ በላይ በጨርቃጨርቅ ንግዱ ላይ እንደበረቱበት ነው ለዘ-ሐበሻ የሚደርሱ መረጃዎች የሚያመላክቱት።

አንዳንድ ምንጮችም የመለስ ዜናዊ አስከሬን ከለውጡ በኋላ ከአዲስ አበባ ስላሴ ቤተክርስቲያን ተወስዶ በትግራይ ስለመቀበሩ ሲናገሩ ቆይተዋል።