የ”ዘመቻ አሉላ” እና የ”መጨረሻው ዘመቻ” መረጃዎች

በትግራይ የተለያዩ አካባቢዎች እየተካሄደ ያለውን ውጊያ ሕወሓት ዘመቻ አሉላ የሚል የሰጠው ሲሆን የኢትዮጵያ ጦር ደግሞ የመጨረሻው ዘመቻ ብሎታል። ትናንት ራሱን የትግራይ ክልል ፕሬዚዳንት አማካሪ ብሎ የሚጠራው ጌታቸው ረዳ ‹‹ከአብይ አህመድ የመጨረሻ ጥቃቶች አንዱ የሆነው የመጨረሻው ጥቃት ከጅምሩ መጥፎ ሆኗል፡፡ ሰራዊቶቹ በሁሉም ግንባር ተሸንፈዋል፡፡ ይህ ለትግራይ ጀግኖች ምርታቸውን የሚሰበስቡበት ወቅት ነው›› ሲል መናገሩን ዘግበን ነበር። ይህንንም በ ዕለቱ የዘ-ሐበሻ ዜና ላይ አቅርበነዋል።

ዛሬ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ይፋ ባደረገው መረጃ ደግሞ በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ ቅጥቀጣ የደረሰበት የጌታቸው ረዳ ጠባቂ ኃይል ክፉኛ ሲመታ ጌታቸው ረዳ ንብረቱን ጥሎ መፈርጠጡን አስታውቋል።

የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ጋዜጠኛው ብርሃኑ ወርቁ ( ከግዳጅ ቀጣና )ያስተላለፈው መረጃ እንዲህ ይላል።

“በተወሰደበት እርምጃ የጁንታው አፈ ቀላጤ ጌታቸው ረዳ ታጣቂ ኃይሉን ብቻ ሳይሆን የመዋጊያ ንብረቶቹንም ጭምር በየቦታው ማዝረክረኩን የ21ኛ ጉና ክፍለ ጦር አስታወቀ ፡፡
የደቡብ ዕዝ 21ኛ ጉና ክፍለ ጦር የሠራዊት አባላት ፣ የማይሰበር እልህና ወኔ ሰንቀው ጁንታው በዕብሪት ተወጥሮ በሀገራችን የጀመረውን ጦርነት በማክሸፍ የሀገራችንን ሉአላዊነት በማስከበር የህግ የበላይነትን እንዲረጋገጥ እያደረጉ እንደሚገኙ የ21ኛ ጉና ክፍለ ጦር ህብረት ዘመቻ ቡድን መሪ ሌ/ኮ ብርሃኑ ኃይሉ ተናግረዋል ።
ሰሞኑን በተደረገው በፈታኝ መሰናክል የታጀበ የአሰሳ ውጊያ ፣ የአካባቢውን አስቸጋሪ ተራራና አቀበት በመጋፈጥ ጠላትን ማፅዳት መቻሉን አረጋግጠዋል ፡፡ በተለይም የጁንታው አፈቀላጤ የሆነው አቶ ጌታቸው ረዳ ሲፈረጥጥ አንጠባጥቧቸውና ደብቋቸው የነበሩትን ወታደራዊ ንብረቶች በቁጥጥር ስር ማዋላቸውን ገልፀዋል።
ከተያዙት ወታደራዊ ንብረቶች ውስጥ ፣ ከዘጠኝ በላይ የመገናኛ ሬዲዮኖች ፣ አስራ ሦስት ካርቶን ባትሪ ፣ መጠናቸው የተለያዩ ሁለት ጀነሬተሮች ፣ አስራ ሁለት ክላሽንኮቭ ጠመንጃ ከሦስት መቶ ጥይትና ከአስር የጥይት ካዝና ጋር በቁጥጥር ስር መዋሉን አረጋግጠዋል ፡፡
ዘመቻ መኮንኑ ፣ ሽብርተኛው በተለያዩ ቦታዎች የደበቃቸው ከ 280 በላይ ኩንታል ጤፍ ፣ ከ 20 ኩንታል በላይ የፊኖ ዱቄት ፣ 120 ብርድ ልብስ ፣ 50 አንሶላን ጨምሮ የተለያዩ ንብረቶች ተይዘዋል ፡፡
ሽብርተኛው ጁንታ በየጊዜው ለጥፋት የሚመለምላቸው ወጣቶችና ሞቶ የተቀበረውን ጁንታ ተመልሶ ይመጣል በሚል ቀቢፀ-ተስፋ የተጠለፉ ሠልጣኝ ምልምሎቹ የሚለብሱት አምስት ከረጢት በላይ አልባሳትና ልዩ ልዩ መገልገያ ቁሳቁሶቹንም በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉን ነናግረዋል ፡፡
የጁንታው ታጣቂ ሃይል ከሲቪል ተቋማትና ግለሰቦች ዘርፏቸው የነበሩ ጤፍ የጫኑ ሁለት የጭነት ተሽከርካሪዎችን አውድመው መሰወራቸውንም ሌ/ኮ ብርሃኑ ኃይሉ ጨምረው ገልፀዋል።
የጁንታው አፈ ቀላጤ ሰራዊቱ አይገባበትም ብሎ ከተማመነበት ሸጥ ድረስ እግር በእግር ተከታትሎ በመዝለቅ ፣ ለፍርድ ያልቀረቡትን ተፈላጊዎች በከፍተኛ እልህ ፣ ወኔና ጀግንነት በማደን ላይ እንደሚገኙ የገለፁት ሌ/ኮ ብርሃኑ ፣ የ21ኛ ጉና ክፍለ ጦር የሰራዊት አባላት የተሰጣቸውን ተልዕኮ ሁሌም ቀን ከሌት በከፍተኛ ሞራል ፣ ዲሲፕሊንና ወታደራዊ ጨዋነት በመፈፀም የላቀ የማድረግ አቅም እንዳላቸው አረጋግጠዋል።”

ጌታቸው ረዳ ይመራው የነበረው እና በአማራ ክልል አቤርጌሌ አቅራቢያ የሚገኘው ኃይል ለ3 ጊዜያት ያህል ወደ አማራ ክልል በመግባት እህል ሲዘርፍ፤ ሰላማዊ ሰዎችን ሲገድል፤ አምቡላንሶችን ሲያቃጥል እንደነበር አይዘነጋም።

ይህ በ እንዲህ እንዳለ ሕወሓት ታጣቂዎች ዘመቻ አሉላ ያሉት ውጊያ በተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች እየተካሄደ መሆኑን የሚገልጹት ምንጭጮች በተለይ በምስራቃዊ እና መከከለኛው ትግራይ የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት የሕወሃትን ታጣቂ እያጸዳ መሆኑን የመከላከያው ምንጮች እየገለጹ ነው።

በሌላ በኩልም ራሱን የሕወሓት ሰራዊት ቃል አቀባይ ብሎ የሚጠራው ገብረ ገብረጻድቃን፤ በአሉላ አባነጋ ስም በተሰየመው ዘመቻ ከሰኔ 11 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ ማጥቃት ጀምረናል ብሎሏል። እስካሁንም ለ13 ጊዜያት ያህል ጥቃት ሰንዝረናል የሚለው ገበረገብረጻድቃን በተለይም ከአላሳ፣ ሃገረ ሰላም፣ በአቢ አዲ አግበ ድረስ ድል ቀንቶናል ሲል ተናግሯል።