በኢትዮጵያ ውስጥ የኢንተርኔት መሰረተ ልማትና የአይቲ ስልጠና በደቡብ ኮሪያው ሲማኡል ንቅናቄ ልምድ እንዲወሰድበት አደርጋለሁ›› – ዶ/ር መኩሪያ

‹‹አንድ ኢትዮጵያዊ ሚኒስትር ከኮሪያ አድቫንስድ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢኒስቲትዩት በዶክትሬት ዲግሪ ተመረቁ›› ሲል ጎንጋ ዶት ኮም ዛሬ ዘግቧል፡፡

እንደዘገባው የተመረቁት አቶ መኩሪያ ሀይሌ ተክለማሪያም ሲሆኑ በአሁኑ ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ አማካሪ ሚኒስትር ናቸው፡፡ ዶክትሬታቸውን ያገኙት በግሎባል ኢንፎርሜሽን ኤንድ ኮሚኒኬሽን ቴክኖሎጂ ፕሮግራም ሲሆን ትምህርቱንም ላለፉት አራት አመታት ሲከታተሉ ቆይተው ባለፈው ወር አጠናቀዋል፡፡ ለመመረቂያ ፅሁፋቸው ያዘጋጁት ርእስ ከፍተኛ ፍጥነት ያለውን ኢንተርኔት ለማዳረስ የሚያስችል ፖሊሲ በሚቀረፅበት ሁኔታ ላይ ነው፡፡

ይህ ፅሁፋቸውም በዩኒቨርስቲው አለም አቀፍ ጆርናል ላይ ታትሞላቸዋል ተብሏል፡፡ ዩኒቨርስቲው እንዳለው ባለፉት አራት አመታት ዶክተር መኩሪያ ያሳዩት ውጤት በጣም የተዋጣለት ነበር፡፡

እሳቸው ለዜና አውታሩ ሲናገሩ ‹‹በኢትዮጵያ ውስጥ የኢንተርኔት መሰረተ ልማትና የአይቲ ስልጠና በደቡብ ኮሪያው ሲማኡል ንቅናቄ ልምድ እንዲወሰድበት አደርጋለሁ›› ብለዋል፡፡ ዶ/ር መኩሪያ ቀደም ሲል የቤቶች ልማትና ኮንስትራክሽን ሚኒስትር እንደነበሩ ይታወቃል፡፡